fbpx

የሐሰት ዜናን በማሰራጨት፣ ከሽንፈት ማገገም አይቻልም!

የሐሰት ዜናን በማሰራጨት፣ ከሽንፈት ማገገም አይቻልም!

(ከኦሮሞ ነፃነት ሠራዊት የተሰጠ መግለጫ)

የአብይ አህመድ ፋሽስታዊ አገዛዝ፣ ሰሞኑን በወሎ ግንባር ያጋጠመውን ከባድ ወታደራዊ ሽንፈት ተከትሎ፣ የመከላከያ ሠራዊቱ መደምሰሱና የተረፈውም የውርደት ሸማውን ተከናንቦ፣ ወደ መሃል አገር በሽሽት መፈርጠጡ ይታወሳል። የአብይ አህመድ አገዛዝም ይሄን በመረዳት፣ ፊንፊኔን ለመመከት በሚል ሰበብ፣ ይሄን ከሞትና ምርኮኛነት ያመለጠ ሠራዊትን በመሰብሰብ፣ ከሚሊሻና ከክልል ልዩ ኃይልና ፖሊስ የተውጣጡ ኃይሎች ጋር በማቀናጀት፣ በአራት ዋና ዋና ግንባሮች፣ ማለትም በጎሐጽዮን፣ በደራ፣ በሸኖ፣ እና በመተሃራ አዲስ ዘመቻ ለማድረግና ሕዝባችንን ለተጨማሪ እልቂት ለማጋለጥ ሌላ የጸረ-ሕዝብና የበቀል ዘመቻ ዝግጅቱን ማጠናቀቁን ተረድተናል። በከሚሴና ዙሪያዋ ባሉ ከተሞችና ሰላማዊ ዜጎቻችን ላይ በቦንብ እና በድሮን የታገዘ የአየር ድብደባ እያካሄደ መሆኑ ይታወቃል። ይሄም፣ ሕዝባችንን ለይቶ በማጥቃት ለስቃይ በመዳረግ፣ በመንግሥታዊ የሽብር ተግባር፣ አንገት ለማስደፋት መሆኑ ይታወቃል። እስካሁን በብርቱ ትግል ሕልውናውን ያስጠበቀውና የመብት ትግሉን በድል የቋጨው የወሎ ሕዝብና የኦሮሞ ነፃነት ጦር፣ አሁንም፣ የአብይ አህመድን የአየር ጥቃት በብቃት መክቶ፣ ለአገር ባለቤትነት የሚደረገውን ትግል በአንጸባራቂ ድል እንደሚያጠናቅቀው እንተማመናለን። ይሄንንም ለሕዝባችን እናረጋግጣለን

ጦራችን፣ በተለያዩ የውጊያ አውዶች እያስመዘገበ ያለውን ድል በመመልከት፣ በተለይም ከትግራይ መከላከያ ሠራዊት (TDF) ጋር ያለንን ስትራቴጂካዊ የትብብር ስምምነትና በተጨባጭ በከሚሴው ውጊያ ላይ የታየውን በጋራ የድርጊት ማቀናጀት እንቅስቃሴ በመገንዘቡ፣ ታላቅ ድንጋጤ ውስጥ ወድቋል። በተጨባጭ መሬት ላይ የተከናነበውን ወታደራዊ ሽንፈት፣ ሙሉ በሙሉ ወደ ስነልቦናዊ ሽንፈት ቀይሮታል።

በመሆኑም፣ ይሄንን አሁን የተከናነበውን ሽንፈት በሐሰት ፕሮፓጋንዳ ወደ ድል ለመቀየር፣ ይሄም ባይቻል፣ የሕዝቡን የአትኩሮት አቅጣጫ ለመቀየር በማሰብ ይመስላል፣ “የትግራይ መከላከያ ሠራዊት እና የኦሮሞ ነፃነት ጦር ተጣልተው፣ እየተታኮሱ ነው” የሚል የፕሮፓጋንዳ ዘመቻ ጀምሮአል።

ሁሉም ሰው ለመረዳት እንደሚችለውና በመሬት ላይ በተጨባጭ ያለውን የትብብርና የድርጊት ቅንጅት የሚታዘብ ሰው እንደሚያውቀው፣ ይሄ የብልጥግና መንግሥት ርካሽ ፕሮፓጋንዳ ፈጽሞ ከእውነት የራቀ ነው።

የትግራይ መከላከያ ሠራዊትና እና የኦሮሞ ነፃነት ጦር፣ ከመቼውም ጊዜ በላይ በመቀራረብ፣ ከወታደራዊ ትብብር ባሻገር፣ ድሕረ-አብይ የሚሆነውን የጊዜያዊ አስተዳደርና የሽግግር ፕሮግራም እያደራጁ ባሉበት በዚህ ወቅት፣ በመካከላቸው ጦር መማዘዝ ይቅርና፣ በሃሳብና በንግግር እንኳን መተላለፍ እንደሌለ ለሕዝባችን ለመግለጽ እንወዳለን።

በሕዝባችንና በሌሎች ጭቁን ሕዝቦች ሁሉ ላይ ታሪክ ይቅር የማይለውን የግፍ እልቂት እየፈጸመ ያለውን የአብይ አህመድን ፋሽስታዊ አገዛዝ ግብዓተ-መሬት ለመፈጸምና የሕዝባችንን የአገር ባለቤትነትና የራስን ዕድል በራስ የመወሰን መብት ለማረጋገጥ ከመቼውም ጊዜ በላይ በቁርጠኝነት እየታገልን እንገኛለን። ወደ ማይቀረው ድልና የሕዝባችንን የዘመናት ምኞት ዕውን ለማድረግ ወደሚያስችለን ግባችንም እየተቃረብን እንደ ሆነ እናምናለን።

ይሄን የተረዳው የአብይ አህመድ ፋሽስታዊ አገዛዝ የሚነዛው የሐሰት ፕሮፓጋንዳ፣ መራራ የሽንፈት ጽዋ የተጎነጩትን ደጋፊዎቹን ለማጽናናትና አራት ኪሎ ላይ ዓይኑን ተክሎ ያለውን የልሂቅ ክፍል ለጊዜው ለማወናበድ ይችል ይሆናል። ነገር ግን ሽንፈትን ወደ ድል ሊቀይር አይችልም። አገዛዙ የደረሰበትን ኪሳራም አይቀንሰውም፣ አይሰርዘውም። ብልጥግናንና ደጋፊ-አደፋፋሪዎቹንም፣ በመሸነፍ ምክንያት ከደረሰባቸው የሞራል ስብራትና የሥነ-ልቦና ቁስል እንዲያገግሙ አያደርግም።

ድል ለኦሮሞ ሕዝብ!
ድል ለተጨቆኑ ሕዝቦች!

Tsegaye_R_Ararssa

6300cookie-checkየሐሰት ዜናን በማሰራጨት፣ ከሽንፈት ማገገም አይቻልም!
%d bloggers like this: